Search

Thursday, November 15, 2012

በኮንዶሚኒየም ቤቶች የታየው ሙስና በ40/60 ፕሮጀክት እንዳይደገም ተጠየቀ

በውድነህ ዘነበ
ባለፉት ዓመታት በተካሄዱ የጋራ መኖርያ ቤቶች ግንባታ ላይ በባለሥልጣናት፣ በኮንትራክተሮችና በአማካሪ ድርጅቶች የተፈጸሙ ሙስናዎች በ40/60 የቁጠባ ቤቶች ፕሮግራም እንዳይደገሙ ተጠየቀ፡፡ ይህ ዓይነቱ አስተያየት ጠንከር ብሎ የቀረበው ከአዲስ አበባ ከተማ በስተምሥራቅ 98 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ በምትገኘው አዳማ ከተማ እየተካሄደ ባለው የኢትዮጵያ የከተሞች ሳምንት ላይ ነው፡፡

ከኅዳር 1 ቀን እስከ 8 ቀን 2005 ዓ.ም. ድረስ በሚዘልቀው የከተሞች ሳምንት ልዩ ልዩ የፓናል ውይይቶች እየተስተናገዱ ሲሆን፣ በአንደኛው የፓናል ውይይቱ ላይ በኮንዶሚኒየም ቤቶች የዕጣ አወጣጥ ነዋሪው ሕዝብ ቤት ሳያገኝ አመራሮች ብቻ ቤት የሚያገኙበት አሠራር ዳግም እንዳይፈጠር በአፅንኦት ተጠይቋል፡፡

በውይይቱ ወቅት የ40/60 ቤቶች ፕሮግራም ግልጽ እንዲሆን ብሎም ግንባታው በአዲስ አበባ ብቻ ሳይሆን በክልል ከተሞችም በተመሳሳይ ወቅት ግንባታው እኩል መጀመር እንዳለበት በተሳታፊዎች ተገልጿል፡፡ በስብሰባው ላይ በከተማ ልማትና ኮንስትራክሽን ሚኒስቴር የመንግሥት ቤቶች ልማትና ኮንስትራክሽን ቢሮ ኃላፊ አቶ አፅብሃ ዮሐንስ እንደገለጹት፣ በ40/60 ቤቶች ልማት ፕሮጀክት ከፌዴራልና ከክልል ባለድርሻ አካላት ጋር የጋራ ግንዛቤ እንዲኖር በአፈጻጸም ወቅት ሊያጋጥም ስለሚችለው ችግር ውይይት ተደርጓል፡፡

ቤቶቹ ጥራትና ደረጃቸውን የጠበቁ እንዲሆኑ ከቻይናና ከደቡብ ኮርያ ተሞክሮ መወሰዱን አቶ አፅብሃ ገልጸው፣ የቤቶቹ ምዝገባ በኢትዮጵያ ንግድ ባንክ አማካይነት በይፋ የሚከናወን በመሆኑ ኅብረተሰቡ በትዕግስት እንዲጠብቅ አስረድተዋል፡፡

የውይይቱ ተሳታፊዎች የቤቶቹ ግንባታ በይፋ ሲጀመር ለነዋሪዎች ግልጽ መሆን እንዳለባቸው፣ ከምንም ነገር በላይ ግልጽነትና ተጠያቂነት ባለበት ሁኔታ የከተማ ልማትና ኮንስትራክሽን ሚኒስቴር እንዲመራው ጠይቀዋል፡፡

ከ1996 ዓ.ም. ጀምሮ ባሉት ዘጠኝ ዓመታት መንግሥት መገንባትና ለተጠቃሚዎች ማስተላለፍ የቻለው 82 ሺሕ ቤቶችን ብቻ ነው፡፡ ለዚህ ግንባታ 13 ቢሊዮን ብር ወጪ ተደርጓል፡፡ በወቅቱ ግንባታው ሲጀመር 453 ሺሕ ሰዎች ተመዝግበው ተጠቃሚ ይሆናሉ ቢባልም፣ ቀሪዎቹ 371 ሺሕ ተመዝጋቢዎች አሁንም ዕድላቸውን በመጠባበቅ ላይ ናቸው፡፡

ነገር ግን በተለያዩ የአስተዳደር ወቅቶች መኖርያ ቤቶችን በዕጣና በምደባ ወይም በዕጣ ብቻ የሚከፋፈሉበት አሠራር በመኖሩ፣ አሠራሩ በፈጠረው ክፍተት ምክንያት በሙስና ያለአግባብ የተጠቀሙ ወይም በሥልጣናቸው ተጠቃሚ የሆኑ እንደነበሩ በየጊዜው የሚነሳ ጉዳይ ነው፡፡

በአዲስ አበባ ከተማ ውስጥ ከአንድ ሚሊዮን በላይ የመኖርያ ቤት እጥረት እንዳለ የሚገመት ከመሆኑም በላይ፣ የ40/60 ቤት ፕሮግራም በቅድሚያ በአዲስ አበባ የሚጀመር በመሆኑ፣ በክልል ከተሞች የሚኖሩ ሰዎች አጋጣሚውን በመጠቀም አዲስ አበባ እየተመላለሱ መሆኑ እየተነገረ ነው፡፡ ከዚህም በተጨማሪ በአዲስ አበባ ዙሪያ ባሉ ከተሞች የራሳቸውን ጎጆ የቀለሱ ሰዎች ሳይቀሩ የ40/60 ፕሮጀክት ተጠቃሚ ለመሆን እየተዘጋጁ መሆናቸውም በኅብረተሰቡ ውስጥ በስፋት ይናፈሳል፡፡ ከዚህም በተጨማሪ መንግሥት ይህንን ፕሮጀክት አስመልክቶ ከኅብረተሰቡ ጋር ውይይት ለማድረግ ማቀዱም እነዚህን ጉዳዮች ለማጥራት ያግዛል እየተባለ ነው፡፡

ከእነዚህ ጭምጭምታዎች በመነሳት ኅብረተሰቡ ምዝገባውን በአንክሮ እየተጠባበቀ ሲሆን፣ በመረጃ እጦት ምክንያት ለውዥንብሮች እየተጋለጠ እንደሆነም በሰፊው እየተነገረ ነው፡፡ በፓናል ውይይቱ ላይ ኅብረተሰቡ ከአሉባልታና ከውዥንብር ራሱን እንዲጠብቅና በትዕግስት የፕሮጀክቱን መጀመር እንዲጠብቅ ቢነገርም፣ የ40/60 የቤት ፕሮጀክት ምዝገባ መጀመርን በንቃት የሚጠባበቁ ነዋሪዎች ግን መንግሥት አስፈጻሚ አካላት ግልጽ እንዲሆኑ አስፈላጊውን ዕርምጃ መውሰድ አለበት እያሉ ነው፡፡

No comments:

Post a Comment