Search

Friday, June 21, 2013

በምንያህል ተሾመ ጉዳይ ለህዝብ ይፋ ያልሆነው ምስጢር!!

በቀጣዩ ዓመት በብራዚል በሚደረገው የዓለም እግር ኳስ ዋንጫ ምድብ ማጣሪያ በምድብ አራት የተደለደለው የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ባለፈው እሁድ አምስተኛ የምድብ ጨዋታውን በአዲስ አበባ ደቡብ አፍሪካን በማሸነፍ ለመጨረሻው ዙር ውድድር ማለፉን ቢያረጋግጥም በተጨዋችነት ተገቢነት ጉዳይ በእጁ የገባውን ዕድል መልሶ ማጣቱን የፌዴሬሽኑ ፕሬዝደንት አቶ ሳህሉ ገ/ወልድ አረጋግጠዋል። ‹‹ስህተት ፈፅመናል›› ሲሉም ተናግረዋል። የብሄራዊ ቡድኑ ተጨዋች ምንያህል ተሾመ ከደቡብ አፍሪካ ጋር ከሜዳ ውጪ ከቦትስዋና ጋር በሜዳችን ላይ በተደረገ ጨዋታ ሁለት ቢጫ ካርድ በማየቱ ምክንያት ከቦትስዋና ጋር በተደረገ የመልስ ጨዋታ ማረፍ ሲገባው ተሰልፎ በመጫወቱ ብሄራዊ ቡድኑ በእጁ የገባውን ዕድል መልሶ ሊያጣ መቻሉን አቶ ሳህሉ በጋዜጣዊ መግለጫ ወቅት አስረድተዋል። በፊፋ ህግ አንድ ተጨዋች ሁለት ቢጫ ካርድ ከተመለከተ አንድ ጨዋታ ማረፍ ይኖርበታል። ይህን ደግሞ የሀገሪቱ እግር ኳስ ፌዴሬሽን ተከታትሎ ማስፈፀም አለበት፡፡ ፊፋ በተለያዩ ምክንያቶች ሳይልክ ቢቀር እንኳን አላሳወክም ተብሎ ሊጠየቅ አይችልም።

ይህም ሆኖ ግን ፊፋ ከቦትስዋናው ጨዋታ 14 ቀን ቀደም ብሎ ምንያህል በቅጣት መሰለፍ እንደሌለበት ለፌዴሬሽኑ አስታውቋል። ባለፈው ረቡዕ ደግሞ መከራከሪያ ነጥብ ካላችሁ በማለት ጉዳዩን በድጋሚ ለማየት ጥያቄ አቅርቧል፡፡ ይሁን እንጂ ፌዴሬሽኑ የመከራከሪያ ነጥብ በማጣቱ ዝምታን መርጧል፡፡ በፊፋ ህግ ለጥያቄው በሁለት ቀን ውስጥ ምላሽ ካልተሰጠ ቅጣቱ ትክክል እንደሆነ ተቆጥሮ ለተጋጣሚው ቡድን ፎርፌ ይሰጣል። በዚህ ህግና ስርዓት መሰረትም ኢትዮጵያ ወደ ቀጣዩ ዙር ለማለፍ የመጨረሻውን የምድብ ጨዋታ ውጤት መጠበቅ ግድ ሆኖባታል፡፡ ኢትዮጵያ አሁንም ከምድቡ ለማለፍ የተሻለው ዕድል አላት። ፌዴሬሽኑ በጉዳዩ ዙሪያ በሰጠው ጋዜጣዊ መግለጫ በመረጃ ልውውጥ ችግር ምክንያት ስህተት ሊፈፀም እንደቻለና ለዚህም የቡድን መሪው አቶ ብርሃኑ ከበደ፤አሰልጣኝ ሰውነት ቢሻውና የአሰልጣኝ ቡድኑ፤ምንያህል ተሾመና አቶ አሸናፊ እጅጉ በምክንያትነት ተጠቅሰዋል። ይሁን እንጂ ቢጫና ቀይ ካርድን ተከታትሎ የማስፈፀምና የማሳወቅ ሀላፊነት ግን የማን እንደሆነ በግልፅ አልተገለፀም። በዋናነት ትኩረት ተሰጥቶት ሲነገር የነበረው ከፊፋ የተላከው መረጃ መድረስ ላለበት አካል ደርሷል አልደረሰም ነው። በትናንቱ ጋዜጣዊ መግለጫ ሁሉም ሃላፊነቴን ተወጥቻለው ከማለት ውጪ ችግሩ የእኔ ነው የሚል ወገን ግን አልተገኘም። በዚህም ምክንያት ፌዴሬሽኑ ጉዳዩን ይበልጥ አጠናክሮ በመመርመር በቅርቡ የቅጣት ውሳኔ እንደሚያሳልፍ አስታውቋል። በትናንቱ ጋዜጣዊ መግለጫ ምንያህል ሁለት ቢጫ ለማየቱ መረጋገጫ ሆኖ የቀረበው ከፊፋ የተላከው መረጃ ብቻ ነው። ከኢትዮጵያ ወገን የቀረበ ወይም የተያዘ ምንም መረጃ የለም። እንደ ፊፋ ሁሉ የብሄራዊ ቡድኑ የአሰልጣኝ ቡድን ለፌዴሬሽኑ ፅህፈት ቤት ወይም ቴክኒክ ክፍል ቢጫና ቀይን በተመለከተ መረጃ ሊሰጥ ቢገባም አልሰጠም። ዋና መረጃ ሊሆን ይገባ የነበረውም ይህ የአሰልጣኝ ቡድኑ የሚያቀርበው መረጃ ነው። ይህ መረጃ ተይዞ ቢሆን ኖሮ ይህ ሁሉ ችግርና ውዝግብ ባልተፈጠረ ነበር። የመረጃ ልውውጡ ባህልና ስርዓት እንዲሁም የጋራ ተጠያቂነቱ ስለሚኖር ምንያህልን በቦትስዋና ጨዋታ ለማሳረፍ የፊፋን ደብዳቤ ባልጠበቅን ነበር፡፡ ቀድሞውኑ መረጃው ስለሚኖር ሰጥተኸኛል አልሰጠኸኝም የሚል ክርክር ባልተነሳ ነበር። የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ተጨዋቾች ሁሌም ቢጫ ለማየታቸው እንደማረጋገጫ እየተደረገ ሲያዝ የነበረው ከፊፋ የሚላከው ደብዳቤ ነው። ግን ስህተት ነው፡፡ ፊፋ ዕሮብ ዕለት ለፌዴሬሽኑ የመከራከሪያ ነጥብ ካላችሁ በማለት ደብዳቤ የላከው ሀገሮች የራሳቸውን ቢጫና ቀይ ካርድ የመያዝ ሃላፊነትና ግዴታ ያለባቸው በመሆኑ ምናልባት የዕለቱ ዳኛ እና ኮሚሽነር ሪፖርት ሲያደርጉ ቁጥር ወይም ስም ተሳስተው ከሆነ በሚል ውሳኔ ከመስጠቱ በፊት ለማጣራት ነው። እዚህ ጋር ነገሩን ይበልጥ ግልፅ ለማድረግ ዘንድሮ በኢትዮጵያ ፕርሚየር ሊግ ቡና ክለብ ላይ የተከሰተውን እናንሳ ፌዴሬሽኑ የ1ኛ ዙር መጠናቀቅን አስመልክቶ በተደረገ ግምገማ ወቅት እያንዳንዱ ክለብ የተመለከተውን ቢጫ ካርድ ለየክለቦቹ ሰጠ በዚህ ሰነድ ላይ የቡናው ሲሳይ ደምሴ የተመለከተው ሦስት ቢጫ ነው ይላል የቡድኑ አሰልጣኞች የያዙት ደግሞ አራት ቢጫ ይላል ክለቡ ፅህፈት ቤት ጋር ያለው ሰነድ ጋር ሲጣራ ደግሞ በርግጥም አራት ቢጫ ሆነ እናም በቀጣይ ጨዋታ ሲሳይ ደምሴ ቡና ከጊዮርጊስ ሲጫወት ሌላ ቢጫ በማየቱ እንዲያርፍ ተደረገ። ይህ ሲሆን ታዲያ ፌዴሬሽኑ ሲሳይ ማረፍ አለበት ብሎ ደብዳቤ አላከም። ነገር ግን በደንቡ መሰረት ቡና ራሱ ተከታትሎ ማሳረፍ ስለነበረበት እንዲያርፍ አድርጓታል፡፡ የምንያህል ጉዳይም መሆን የነበረበት እንዲህ ነው። ከፊፋ በላይ መረጃው ሊኖር የሚገባው ፌዴሬሽኑ ጋር በተለይም የአሰልጣኝ ቡድኑ ጋር ነው፡፡ ምንያህል በቦትስዋና ጨዋታ ተገቢ ተጨዋች እንዳልሆነ ለማወቅ የፊፋን ደብዳቤ መጠበቅ ባላስፈለገ ነበር። ይህ ሃላፊነት በዋናነት ደግሞ ሊሆን የሚገባው የዋና አሰልጣኙ ነው፡፡ በየትኛውም ክለብ ያለው አሰራር ይህ ነው፡፡ ዋናው አሰልጣኝ ይህን ሃላፊነት መዝግቦ እንዲይዝ የጨዋታ ቀን ለረዳት አሰልጣኙ ወይም ለቡድን መሪው ይሰጣል። ከጨዋታው በኋላም ያንን በመቀበል በራሱ ሰነድ ላይ ያሰፍራል ግልባጩንም ከሌሎች የጨዋታ ሪፖርቶች ጋር አያይዞ ለቴክኒክ ክፍሉ ወይም ለፅህፈት ቤቱ ያሳውቃል፡፡ በኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ውስጥ የነበረው አሰራር ግን ከእዚህ የተለየ ነው፡፡ ዋናው አሰልጣኝም ሆነ ረዳቱና የቡድን መሪው የጨዋታ ቀን ቢጫና ቀይን በተመለከተ ምንም አይነት መረጃ እንደማይዙና ይህ ብቻ አይደለም ስለ እያንዳንዱ ጨዋታና ተጨዋች በተመለከተ ለፌዴሬሽኑ ሪፖርት እንደማያቀርቡና በፌዴሬሽኑ በኩልም የመጠየቁ ባህል እንደሌለ ባደረግነው ማጣራት ለማረጋገጥ ችለናል፡፡

አሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው የብሄራዊ ቡድን አሰልጣኝ ከሆኑ ሁለት ዓመት የሞላቸው ቢሆንም ማን ምን ያህል ተጫወተ የሚሉና መሰል ጥያቄዎች ቢጠየቁ መረጃ በግለሰቦች እንጂ በፌዴሬሽኑ የለም፡፡ ለብሄራዊ ቡድኑ በሚሊዮን የሚቆጠር ብር ይወጣል ያ ሁሉ ብር የወጣበት ውድድርና መረጃ ግን በስርዓትና በተደራጀ መልኩ ተይዞ አይቀመጥም፡፡ የብሄራዊ ቡድኑ ሃላፊነት ሙሉ ለሙሉ ለአቶ ሰውነት ቢሰጥም በተመዘገበው ጥሩም ሆነ መጥፎ ውጤት ዙሪያ የፌዴሬሽኑ ሃላፊዎች ከአሰልጣኙ ጋር በየጊዜው ግምገማና ውይይት አያደርጉም፡፡ እንዲያውም በተወሰነ ደረጃም ቢሆን የብሄራዊ ቡድኑን የአሰልጣኞች ቡድን እንቅስቃሴ በቅርብ የሚከታተለው ከፌዴሬሽኑ ይልቅ የፌዴራል ስፖርት ኮሚሽን ነው፡፡ የፌዴሬሽኑ ስራ አስኪያጅ ኮሚቴ ሰኞ ዕለት ከቀኑ 10፡00ሠዓት እስከ ምሽት 2፡30 ሠዓት ድረስ በጉዳዩ ዙሪያ ከሚመለከታቸው አካላት ጋር ሰፊ ውይይትና ግምገማ አድርጓል፡፡ በዚህ ወቅትም የምንያህልን ቢጫ በተመለከተ ፊፋ ከላከው ውጪ በአሰልጣኝ ቡድኑ አባላት ወይም በፌዴሬሽኑ ፅህፈት ቤት የተያዘ መረጃ እንዳለ ጠይቋል። ከማንም ምንም ሊቀርብ ግን አልቻለም፡፡ የፌዴሬሽኑ አመራሮች በቁጣ የአሰልጣኝ ቡድኑን አባላት እና ፅህፈት ቤቱን እንዴት የራሳችሁን መረጃ አትይዙም ሃላፊነቱስ የማን ነው ሲሉ ጠይቀዋል፡፡ በዚሁ ወቅትም ይህ ሃላፊነት የአሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው መሆኑ ተገልፆል፡፡ አሰልጣኝ ሰውነት ከቅጥር ውላቸው ጋር ተያይዞ በተሰጣቸውና ሐምሌ 1/2004ዓ.ም ፈርመው በወሰዱት የስራ መዘርዝር ተራ ቁጥር 20 በኢንተርናሽናል ውድድር ወቅት ቢጫና ቀይ ካርድን በተመለከተ ተከታትሎ መዝግቦ የመያዝና የማስወሰን ሃላፊነት የእሳቸው መሆኑ ሰፍሯል። አሰልጣኝ ሰውነት ግን የስራ መዘርዝሩን እንዳላዩትና ሃላፊነቱም የእሳቸው ሊሆን እንደማይገባ ይዘው እንደማያውቁና ወደፊትም እንደማይዙ ተናግረዋል የፌዴሬሽኑ ሃላፊዎችም በአሰልጣኙ ንግግር ክፉኛ በመቆጣት አምርረው ምላሽ ሰጥተዋል፡፡ የእኛን ተጨዋቾች ብቻ ሳይሆን የተጋጣሚ ተጨዋቾችን ቅጣት ሳይቀር ተከታትለህ ልትይዝ ይገባል በማለት ሁሉም አቋም ሲይዙ አቶ ሰውነት ጉዳዩን እንዳለሳለሱት ከታማኝ ምንጮች ያገኘነው መረጃ ያመለክታል። በጉዳዩ ዙሪያ የፌዴሬሽኑ ፕሬዝደንቶችና ዋና አሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው አስተያየት እንዲሰጡን ተንቀሳቃሽ ስልካቸው ላይ በተደጋጋሚ ብንደውልም ምላሽ ልናገኝ አልቻልንም። ሰኞ ዕለት በተደረገው ውይይትና ግምገማ ቢጫና ቀይ ካርድን መዝግቦ የመያዙ ሃላፊነት ለማን እንደተሰጠና መሠረታዊ ችግሩ ምን እንደሆነ ቢታወቅም ይህ ግን በትናንቱ ጋዜጣዊ መግለጫ ወቅት ይፋ አልተደረገም፡፡ በማንም በኩል ይፋ እንዳይደረግና በምስጢር እንዲያዝም ትዕዛዝ እንደተሠጠ ከታማኝ ምንጮቻችን ለማወቅ ችለናል፡፡ ይህ በእንዲህ እንዳለ በተፈጠረው ስህተት ዙሪያ የፌዴራል ስፖርት ኮሚሽን ትናንት የፌዴሬሽኑን ከፍተኛ ሃላፊዎች ጠርቶ አነጋግሯል፡፡ የስፖርት ኮሚሽን ኮሚሽነር አቶ አብዲሳ ያደታ ትናንት ረፋድ ላይ የፌዴሬሽኑን ሃላፊዎች በፅህፈት ቤታቸው ረዥም ሰዓት በመውሰድ በጉዳዩ ላይ ማብራሪያና መረጃ እንዲሰጡዋቸው ጠይቀዋል። ይሁን እንጂ ምን ውሳኔ እንዳሳለፉ ጥረት ብናደርግም ለማወቅ አልቻልንም።

No comments:

Post a Comment