Search

Monday, February 11, 2013

አንጋፋው ድምጻዊ ታምራት ሞላ ከዚህ አለም በሞት ተለየ

አንጋፋው ድምጻዊ ታምራት ሞላ ዛሬ ንጋት ላይ ከዚህ አለም በሞት ተለየ።
አርቲስት ታምራት ሞላ በ19 36 ዓ.ም ከአባቱ ከፊት አውራሪ ሞላ ዘለለውና ከእናቱ ከወይዘሮ አበራሽ የኔነህ ፥ በጎንደር ከተማ ተወለደ ።
በ19 53 ዓ.ም ከጎንደር ወደ አዲስ አበባ ከአጎቱ ጋር በመምጣት በክቡር ዘበኛ የልጅ ወታደር በመሆን የሙዚቃውን አለም አሃዱ ብሎ ጀመረ።
በ19 55 ዓ.ም አብዛኛውን የሙዚቃ ህይወቱን ያሳለፈበትን የምድር ጦር ሰራዊትን የተቀላቀለው አርቲስት ታምራት ፥ ሃገራዊ ፣ ማህበራዊ እና ፍቅርን መሰረት ያደረጉ ሙዚቃዎችን ከመጫወቱ ባለፈ ድራማ እና ቲያትርን ምክንያት አድርጎ መድረክ ላይ መቆም መቻሉን ታሪኩ ያስረዳል።
በተለይም ትግላችን በሚል ቲያትር በመሪ ተዋናይነት ለመጫወቱም ባለፈ ፥ የበርካታ ዜማዎች ድርሰትን ቀምሮ ለህዝብ አቅርቧል።
በሃገር ፍቅር ቲያትር ቤት ለረጅም ጊዜያት በድምጻዊነት ያገለገለው አርቲስት ታምራት ፥ ከ50 አመታት በላይ ባስቆጠረው የሙዚቃ ህይወቱ ከአድማጭ ጆሮ የማይጠፉና የማይረሱ ሙዚቃዎችን ተጫውቷል።
አርቲስት ታምራት በተለያዩ ሃገራዊ ተሳትፎዎች ላይ ኪነ ጥበቡን በመወከል በሙያው ሃገሩን አገልግሏል።
በተለይም በኢትዮ- ኤርትራ ጦርነት ወቅት ከሙያ አጋሮቹ ጋር በመሆን ፥ በአውደ ውጊያው ተገኝቶ የጦር ሰራዊቱን ሲያበረታታ ነበር።
አርቲስት ታምራት ከአራት አመት በፊት ባጋጠመው ህመም ሳቢያ በአሜሪካ እና በታይላንድ ህክምናውን ሲከታተል ቢቆይም ፥ ዛሬ ንጋት ላይ በተወለደ በ69 አመቱ ከዚህ አለም በሞት ተለይቷል።
አርቲስት ታምራት ባለ ትዳር እና የ3 ወንድ እና የ2 ሴት ልጆች አባት ነበር።
የቀብር ስነ ስርዓቱ ዛሬ በ 10 ሰአት በመንበረ ፀባኦት ቅድስት ስላሴ ካቴድራል ቤተሰቦቹ ፣ ወዳጅ ዘመዶቹ ፣ የሙያ አጋሮቹ እና አድናቂዎቹ በተገኙበት ይፈጸማል።

No comments:

Post a Comment