Search

Wednesday, July 8, 2015

የግል ባንኮች ትርፍ ከአምስት ቢሊዮን ብር በላይ እንደሚሆን ይጠበቃል

የግል ባንኮች ትርፍ ከአምስት ቢሊዮን ብር በላይ እንደሚሆን ይጠበቃል

የግል ባንኮች ትርፍ ከአምስት ቢሊዮን ብር በላይ እንደሚሆን ይጠበቃል
-ንግድ ባንክ ከታክስ በፊት 12 ቢሊዮን ብር ማትረፉ ተሰምቷል
በኢትዮጵያ የባንክ ኢንዱስትሪ ውስጥ የሚንቀሳቀሱ 16 የግል ባንኮች በ2007 በጀት ዓመት ከታክስ በፊት ከአምስት ቢሊዮን ብር በላይ ትርፍ እንደሚያገኙ ሲጠበቅ፣ አንዳንድ ባንኮችም የትርፍ ምጣኔያቸውን ከእጥፍ በላይ ማሳደጋቸው ታወቀ፡፡ 
የ2007 ዓ.ም. የባንኮቹ የመጀመሪያ ደረጃ ጥቅል መረጃ እንደሚያሳየው ሁሉም ባንኮች በአትራፊነታቸው ዘልቀዋል፡፡ ከአምናው የበለጠ ትርፍ ማግኘትም ችለዋል፡፡ ባለፈው ዓመት ሁሉም ባንኮች ከታክስ በፊት አትርፈውት የነበረው ግርድፍ ትርፍ ከ4.6 ቢሊዮን ብር በላይ መሆኑ ይታወሳል፡፡
ሁሉም የግል ባንኮች በ2007 በበጀት የሒሳብ ሪፖርት ተቀናናሽ ሒሳብ ቢኖርባቸውም፣ ጥቅል ትርፋቸው ከአምስት ቢሊዮን ብር በላይ ይሆናል ተብሎ እየተጠበቀ ነው፡፡ በዚሁ መሠረት ከፍተኛ ትርፍ በማግኘት ዘንድሮም ከግል ባንኮች ከፍተኛውን ትርፍ ያስመዘገበው ዳሸን ባንክ ሲሆን፣ ከታክስ በፊት ከ950 ሚሊዮን ብር በላይ ማትረፉ ተጠቁሟል፡፡ በ2006 ዓ.ም. ባንኩ ከታክስ በፊት 928 ሚሊዮን ብር ማትረፉ አይዘነጋም፡፡
አዋሽ ባንክም ወደ 890 ሚሊዮን ብር ገደማ ማትረፉ እየተነገረ ነው፡፡ ካለፉት ሦስት ዓመታት ወዲህ ከግል ባንኮች በትርፍ መጠኑ ወደ ሦስተኛ ደረጃ ላይ የመጣው የኦሮሚያ የኅብረት ሥራ ባንክ ከ600 ሚሊዮን ብር በላይ በማትረፍ ደረጃውን ይዞ መቀጠሉ ታውቋል፡፡
በበጀት ዓመቱ በትርፍ ምጣኔው ከፍተኛ ዕድገት ካሳዩ ባንኮች መካከል እናት ባንክ አንዱ ሲሆን፣ በበጀት ዓመቱ ከ72 ሚሊዮን ብር በላይ ማትረፍ ችሏል፡፡ ይህ ትርፍ ባለፈው በጀት ዓመት ካገኘው ትርፍ ጋር በንፅፅር ሲቀመጥ ከእጥፍ በላይ ማደጉን ያሳያል፡፡ ባንኩ በ2006 በጀት ዓመት አስመዝግቦት የነበረው ትርፍ 31 ሚሊዮን ብር እንደነበር ይታወሳል፡፡
እንደ እናት ባንክ ሁሉ ከአምናው የትርፍ ምጣኔ ጋር ሲነፃፀር ከ50 በመቶ በላይ ብልጫ ያለው ትርፍ ያስመዘገበው አንበሳ ባንክ ነው፡፡ እንደ ምንጮች ገለጻ የአንበሳ ባንክ በ2007 ዓ.ም. ያልተጣራ ትርፍ 275 ሚሊዮን ብር ደርሷል፡፡ ይህ ትርፍ አምና አስመዝግቦት ከነበረው 127 ሚሊዮን ብር ጋር ሲነፃፀር ከ145 ሚሊዮን ብር በላይ ጭማሪ አሳይቷል፡፡ 
አንበሳ ባንክ በትርፍ ዕድገቱ ብቻ ሳይሆን 580 ሚሊዮን ብር የነበረውን የተቀማጭ ገንዘብ አቅሙን ወደ 1.7 ቢሊዮን ብር በማድረስ ከፍተኛ ለውጥ ማስመዝገብ መቻሉ ይጠቀሳል፡፡
ብርሃን ኢንተርናሽናል ባንክ በ2006 ዓ.ም. 131 ሚሊዮን ብር የነበረውን ትርፍ ወደ 140 ሚሊዮን ብር ማድረስ ችሏል፡፡ ንብ ባንክ ከ430 ሚሊዮን ብር በላይ እንዳተረፈ ሲነገር፣ አምና 350 ሚሊዮን ብር ያተረፈው አቢሲኒያ ባንክ ደግሞ ከ365 ሚሊዮን ብር በላይ ማትረፉ ተጠቁሟል፡፡ ደቡብ ግሎባል ባንክም ከአምናው በተሻለ ከታክስ በፊት 31 ሚሊዮን ብር ማትረፍ ችሏል፡፡ ይህ ትርፍ ከሁሉም ባንኮች ያነሰ ነው፡፡ ባንኩ አምና ያገኘው ትርፍ 19 ሚሊዮን ብር ነበር፡፡
ሌሎቹም ባንኮች የትርፍ ምጣኔያቸው ዕድገት የተለያየ ቢሆንም፣ የትርፍ ዕድገት በማሳየታቸው በአጠቃላይ የግል ባንኮችን የትርፍ መጠን አምና ከነበረበት ከግማሽ ቢሊዮን ብር በላይ ያሳድገዋል ተብሎ እየተጠበቀ ነው፡፡ 
የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በ2007 በጀት ዓመት 12 ቢሊዮን ብር ከታክስ በፊት ማትረፉ ተሰምቷል፡፡ ንግድ ባንክ ባለፈው ዓመት 9.7 ቢሊዮን ብር ከታክስ በፊት ማትረፉ ይታወሳል፡፡ የዘንድሮው ግን ትልቅ ትርፍ መሆኑ ተጠቁሟል፡፡ 

No comments:

Post a Comment